Asset Publisher

null ከጋራ ገቢዎች ከ34.6 ቢሊዮን ብር በላይ ለክልሎች ተላለፈ

የፌደራልና የክልል መንግሥታት የጋራ ገቢዎች ተብለው ከተወሰኑት የታክስ አይነቶች በ2014 በጀት ዓመት በተቀመጠው የገቢ ማከፋፈያ ቀመር መሠረት 34ቢሊዮን 692ሚሊዮን 318ሺ 500 ብር ለክልሎች እንዲተላለፍ መደረጉን የገቢዎች ሚኒስትር አቶ ላቀ አያሌው ገለጹ፡፡
የሚተላለፈው የብር መጠን ከጊዜ ወደጊዜ ከፍተኛ እድገት እያሳየ መምጣቱን የጠቀሱት ሚኒስትሩ፤ የጋራ ገቢዎች የማከፋፈያ ቀመር ከመሻሻሉ በፊት በ2012 በጀት ዓመት 4ቢሊዮን 179ሚሊየን 843ሺ 961 ብር፤ ቀመሩ ከተሻሻለ በኋላ ባሉ ተከታታይ ዓመታት ማለትም በ2013 በጀት ዓመት 22ቢሊዮን 554ሚሊየን 130ሺ 784 ብር እንዲሁም በዘንድሮ በጀት ዓመትም 34ቢሊዮን 692ሚሊዮን 318ሺ 500 ብር እንዲተላለፍ ተደርጓል ብለዋል፡፡
በተጨማሪም የ2014 በጀት ዓመት በ2012 በጀት ዓመት ተላልፎ ከነበረው ጋር ሲነጻጸር የብር 30ቢሊዮን 512ሚሊየን 474ሺ 538 እድገት ወይም የ730 በመቶ ዕድገት ያለው ሲሆን፤ በ2013 በጀት ዓመት ተላልፎ ከነበረው ደግሞ የብር 12ቢሊዮን 138ሚሊየን 187ሺ 715 ወይም የ53.82 በመቶ እድገት እንዳለው አቶ ላቀ አሳውቀዋል፡፡
ሚኒስትሩ የጋራ ገቢዎች የማከፋፈያ ቀመር መሻሻል፣ የገቢ አሰባሰባችን አቅም መጨመር እና ክፍፍሉ በተቀመጠው ቀመር መሠረት መሠራቱ ለሚተላለፈው ገቢ ዕድገት ዋነኛ ምክንያቶች መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡
በመጨረሻም ለዚህ መልካም ስራ ስኬት በቅንነትና በቁርጠኝነት የሰሩትን የገቢዎች ሚኒስቴር አመራሮችና ሰራተኞች፣ ግብር ከፋዩ ማህበረሰብ እንዲሁም ድጋፍ ያደረጉ አጋር አካላት በራሴና በገቢዎች ሚኒስቴር ስም ምስጋና ይድረሳችሁ ብለዋል፡፡