ሀገራዊ ጥሪን ተቀብለው ወደ ኢትዮጵያ እየገቡ ላሉ ዲያስፖራዎች ፈጣን አገልግሎት እየተሰጠ ነው
የጉምሩክ ኮሚሽን ከተለያዩ ዓለም ሀገራት ሀገራዊ ጥሪን ተቀብለው ወደ ኢትዮጵያ እየገቡ ላሉ መንገደኞች የተለየ የጉምሩክ አገልግሎት መስጫ ቦታ በማዘጋጀት ፈጣን አገልግሎት እየሰጠ እንደሆነ በጉምሩክ ኮሚሽን የአዲስ አበባ ቦሌ ኤርፖርት ጉምሩክ ቅ/ፅ/ቤት የመንደገኞች ጉዳይ ም/ስራ አስኪያጅ አቶ ዘራኤል ለአ ገልፀዋል፡፡
የህክምና ቁሳቁስ እና ሌሎች ድጋፎችን ይዘው የሚመጡ መንገደኞችም ያመጡትን ድጋፍ በቀላሉ ለማስረከብ እንዲያመቻቸው ከጤና ሚኒስቴር እና ሌሎች አጋር አካላት ጋር በመተባበር እና መጋዘን በማዘጋጀት አገልግሎት እየተሰጠ እንደሆነ ም/ስራ አስኪያጁ አክለው ገልፀዋል፡፡
ሀገራዊ ጥሪን ተቀብለው ወደ ኢትዮጵያ እየገቡ ያሉ ዲያስፖራዎችን በተገቢው ሁኔታ ለማስተናገድ በቂ ቅድመ ዝግጅት በማድረግ እና ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመቀናጀት እንዲሁም የተለያዩ ኮሚቴዎችን በማዋቀር የ24 ሰዓት ፈጣን አገልግሎት እየተሰጠ እንደሆነ የገለፁት ደግሞ የቅ/ፅ/ቤቱ የኢንተርናሽናል መንገደኞች ቡድን አስተባበሪ አቶ ዝያድ ኑረታ ናቸው፡፡
ዲያስፖራዎች ወደ ኢትዮጵያ ይዘው የመጡትን የተለያዩ ሀገራት ገንዘቦች በህጋዊ መንገድ በመመንዘር ሀገራችን በቂ የውጭ ምንዛሬ እንድታገኝ የበኩላቸውን አተዋፅኦ እንዲያበረክቱም ቡድን አስተባባሪው መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡
ሀገራዊ ጥሪን ተቀብለው ከአሜሪካ ኮሎንበስ ግዛት የመጡት ወ/ሮ ውበት በላቸው እና አቶ አጋር ወልዴ የተባሉ ዲያስፖራዎች በበኩላቸው በተደረገላቸው መልካም አቀባበልና ፈጣን የጉምሩክ አገልግሎት መደሰታቸውን ገልፀው በቆይታቸው የተለያዩ የኢንቨስትመንት አማራጮችን በማጤን እና ኢንቨስት በማድረግ ሰፊ የስራ እድልን ለመፍጠር እምዲሁም ምርቶችን ወደ ውጭ ሀገራት በመላክ ሀገራችን በቂ የውጭ ምንዛሬ እንድታገኝ እንደሚሰሩም ጠቁመዋል፡፡