የ2017 በጀት ዓመት አፈጻጸምን ስኬታማ ለማድረግ እንደሚሰራ ተገለጸ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ512 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ተሰብስቧል
ሐምሌ 18/2016 ዓ.ም (የገቢዎች ሚኒስቴር)
በገቢዎች ሚኒስቴር የታክስ ስርዓት ዘርፍ የ2016 በጀት ዓመት እቅድ አፈጻጸም ግምገማ እና የ2017 በጀት ዓመት እቅድ ላይ ውይይት እያካሔደ ይገኛል።
በመድረኩ የገቢዎች ሚኒስቴር የታክስ ስርዓት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ተስፋዬ ቱሉ እንዳሉት የ2016 በጀት ዓመት እቅድ ከባለፉት ዓመታት አንጻር ከፍተኛ ቢሆንም በገቢ አሰባሰብ ጥሩ አፈጻጸም ማስመዝገብ መቻሉን ገልጸዋል፡፡ ለእቅዱ መሳካትም ከሁሉም ሰራተኛ ውጤታማ እርብርብ በተጨማሪ አስቻይ ሁኔታዎችን በሚገባ መለየት መቻሉ፣ ተቋማዊ ሪፎርም ተጠናክሮ መሰራቱ፣ የሕግ ማስከበር ስራው ውጤታማ መሆኑ፣ የታክስ እና ጉምሩክ ንቅናቄ በትኩረት መሰራቱ ውጤታማ የታክስ አሰባስብ እንዲኖር ጉልህ ሚና ነበረው ብለዋል።
አያይዘውም የ2017 በጀት ዓመት እቅድን ማሳካት የሚቻለው በዋነኝነት የሁሉም የተቋሙ ሰራተኛ ርብርብ ሲኖር መሆኑን በመገንዘብ አመራሩ እና ፈጻሚው በእቅዱ ላይ በንቃት ተወያይቶ የጋራ እቋም በመያዝ ውጤታማ እንደሚያደርግ ያላቸውን ጽኑ እምነት ገልጸዋል።
በመድረኩ ላይ በሚኒስቴሩ የታክስ ስርዓት ዘርፍ አማካሪ አቶ ሂካ ባርባ የዘርፉን የ2016 በጀት ዓመት እቅድ አፈጻጸም ሪፓርት ለውይይት አቅርበዋል።
ሐምሌ 21/ 2016 ዓ.ም (ገቢዎች ሚኒስቴር)
የገቢዎች ሚኒስቴር እና የጉምሩክ ኮሚሽን በ2016 በጀት ዓመት የዕቅድ አፈጻጸም እና በ2017 በጀት ዓመት ዕቅድ ዙሪያ በአርባምንጭ ከተማ ውይይት በማካሄድ ላይ ይገኛሉ፡፡
በመድረኩ በተጠናቀቀው የ2016 በጀት ዓመት 529.3 ቢሊዮን ብር ለመሰብሰብ ታቅዶ ከ512 ቢሊዮን ብር በላይ መሰብሰብ መቻሉን የገቢዎች ሚኒስትር ወ/ሮ ዓይናለም ንጉሴ ገልጸዋል፡፡
ከአምናው በጀት ዓመት ጋር ሲነፃፀር ገቢው ከ70 ቢሊዮን ብር በላይ ብልጫ እንዳለውም ገልፀዋል፡፡
ሚኒስትሯ አክለውም ዘመናዊ እና ተደራሽ የታክስና የጉምሩክ አስተዳደር ስርዓትን በመገንባት አዳዲስ አሰራሮችን በመቅረፅ እንዲሁም በዘመናዊ ቴክኖሎጂ በመደገፍ ገቢ አሰባሰቡን ውጤታማ በማድረግ የዕቅዱን ከ96 በመቶ በላይ እንዲሳካ አስችሏል ብለዋል፡፡
በበጀት ዓመቱ ህገወጥ ንግድ እና ኮንትሮባንድ በሀገራዊ የገቢ አሰባሰብ ስርዓቱ ላይ የጎላ ተፅዕኖ እንዳሳረፈ ገልፀው፤ በቀጣይ በጀት ዓመት ሁሉም ባለድርሻ አካላት ህጋዊነትን ለማስፈን በሚደረገው ጥረት ትብብር እንዲያደርጉ ሚኒስትሯ ጥሪ አቅርበዋል፡፡